top of page

እማ!

 

ካንቺ ከተዘራው ካንቺ ከተገኝው ከዚያች ዐጥቢያ አንስቶ:

በልግዋም እንዳለ ድምፅ እንደሌለው ሰው ልሳኔ ተዘግቶ:

ከቶ ያልነገርኩሽ ልነግርሽ የምሻው አንድ ምስጢር አለኝ:

ላመታት ተረግዞ በውስጤ የኖረ አልወጣልህ ያለኝ::

 

ደከመኝ ሰለቸኝ በቅቶኛል ማታውቂ:

ከዐለት የፀናሽ እንደ እስራኤል ሳምሶን ጠንካራ ነሽ አንቺ::

ዐለም ወረተኛ ፊትዋን አዙራብሽ መከራ ቢበዛ:

መሸነፍ አታውቂም እጅ መስጠት የለም እንዲሁ እንደዋዛ:

ሰው እንዳሸን በዝቶ ካለበት ከተማ:

ወገን አልባ ሁነሽ ስቃይሽ ቢጠና:ችግርን ተካፋይ ብታጪም ሁነኛ:

አንቺ ግን:

«ያለሰው አይኖርም» ብለሽ እየመከርሽ አሳድገሽናል:

ማክበር-የመከበር መውደድ-የመወደድ ዋጋ እንደሆኑ አስተምረሽናል::

ራስ ወዳዶች በዝተው በሞሉት ከተማ:

መሽቀርቀር ሳያምርሽ ሁነሽ ራስ አልባ:

ህይወትሽን ሙሉ ካብራክሽ ለወጣን ለኛ ለልጆችሽ ሰውተሽ ስትኖሪ:

አንዲት ቅዕበት እንክዋ በፈተና ታጠፈሽ ወድቀሽ ሳትቀሪ:

አቀበቱን ወጥተሽ ቁልቁለቱን ወርደሽ ላብሽን አንጠፍጠፈሽ ባኖርሽው መሰረት:

ይሀው እኛ ዛሬ ሰውነትን ወርሰን ጥንካሬን ለብሰን መሰረትን ህይወት::

ታዲያ ለሰጠሽን ተመን ለማይገልጠው ዋጋ አልባ በረከት

ቃላት አጥቼለት:እስካሁን ሳልነግርሽ ከልቤ አምቄ ደብቄሽ ያኖርኩት: አንድ ምስጢር አለኝ ቅድም ብዬሻለሁ:

እሱም:

እጅጉን አድርጌ:

እጅጉን አድርጌ: በጣም ወድሻለሁ!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!

 

ታደለ ወርቁ (የ ባህራን)

መታሰቢያነቱ፥ ለእናቴ

17 ጥር 2008

bottom of page